ምድራዊ ሊቀ ካህናት
1ሊቀ ካህናት ሁሉ ስለ ኀጢአት መባንና መሥዋዕትን ሊያቀርብ ከሰው ተመርጦ ለእግዚአብሔር በሆነው ነገር ሁሉ ስለ ሰው ይሾማልና። 2እርሱ ራሱም ደካማ ነውና ባለማወቃቸው ከሳቱ ሰዎች ጋር መከራን ሊቀበል ይችላል። 3በዚህም ምክንያት ስለ ሕዝብ እንደሚያቀርብ እንዲሁ ስለ ራሱ ደግሞ መሥዋዕትን ስለ ኀጢአት ማቅረብ ይገባዋል። 4እንደ አሮንም በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር፥ ማንም ለራሱ ክብርን የሚወስድ የለም። 5እንዲሁ ክርስቶስም ሊቀ ካህናት ይሆን ዘንድ ራሱን ያከበረ አይደለም፤ ነገር ግን፥ “አንተ ልጄ ነህ፥ እኔም ዛሬ ወለድሁህ” ያለው እርሱ ራሱ ነው። 6ዳግመኛም፥ “እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት የዘለዓለም ካህን አንተ ነህ” ይላል። 7እርሱም ሥጋ ለብሶ በዚህ ዓለም በነበረበት ጊዜ፥ በታላቅ ጩኸትና እንባ ከሞት ሊያድነው ወደሚችለው ጸሎትንና ምልጃን አቀረበ፤ ጽድቁንም ሰማው። 8ልጅም ቢሆን መከራን ስለ ተቀበለ መታዘዝን ዐወቀ። 9ከተፈጸመም በኋላ ለሚታዘዝለት ሁሉ ሕይወትን የሚሰጥ የዘለዓለም መድኅን ሆነ። 10እግዚአብሔርም እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት የዘለዓለም ሊቀ ካህናት አለው። 11ስለ እርሱም የምንናገረው ብዙ ነገር አለን፤ ጆሮዎቻችሁም ስለ ፈዘዙ በቃል ልንተረጕመው ጭንቅ ነው። 12መምህራን ልትሆኑ ሲገባችሁ፥ ካመናችሁ ጀምሮ በትምህርት ላይ የቈያችሁ ስለ ሆነ፥ እስከ ዛሬም ገና የእግዚአብሔርን የቃሉን መጀመሪያ ትምህርት ሊያስተምሩአችሁ ትወዳላችሁ፤ ወተትንም ሊግቱአችሁ ትሻላችሁ፤ ጽኑ ምግብንም አይደለም። 13ወተትን የሚጋት ሁሉ ሕፃን ስለሆነ፥ የጽድቅን ቃል ሊያውቅ አይሻም። 14ጠንካራ ምግብ ግን መልካሙንና ክፉዉን ለመለየት በሥራቸው የለመደ ልቡና ላላቸው ለፍጹማን ሰዎች ነው።