ቅዱስ ጳውሎስ ሁለተኛ ወደ ኢየሩሳሌም ስለ መውጣቱ
1ከዐሥራ አራት ዓመትም በኋላ ከበርናባስ ጋር እንደ ገና ወደ ኢየሩሳሌም ወጣሁ፤ ቲቶንም ይዠው ሄድሁ። 2እንደ ተገለጠልኝም ወጣሁ፤ በከንቱ እንዳልሮጥ፥ ወይም በከንቱ ሮጬ እንዳልሆነ፥ በአሕዛብ መካከል የምሰብከውን ወንጌል አለቆች መስለው ለሚታዩት አስታወቅኋቸው። 3አብሮኝ የነበረው ቲቶም አረማዊ ሲሆን እንዲገዘር ግድ አላልሁትም። 4ይኸውም ባሪያዎች ያደርጉን ዘንድ በኢየሱስ ክርስቶስ ያገኘናትን ነጻነት ሊሰልሉ በስውር ወደ እኛ የገቡ ሐሰተኞች መምህራንን ደስ አይበላቸው ብዬ ነው። 5ለምንም ይሆናሉ ብለን የማናስባቸው ናቸው፤ እውነተኛው ትምህርት በእናንተ ይጸና ዘንድ አንዲት ሰዓትም እንኳ አልተገዛንላቸውም። 6አለቆች የመሰሉት ግን ቀድሞ እነርሱ እንዴት እንደ ነበሩ ልናገር አያገደኝም፤ እግዚአብሔር ለሰው ፊት አያዳላምና፤ አለቆች የመሰሉትም ከራሳቸው ምንም ነገር የጨመሩልኝ የለምና። 7የጴጥሮስ ትምህርት በተገዘሩ በአይሁድ ዘንድ እንደ ታመነለት፥ የእኔም ትምህርት ባልተገዘሩ በአሕዛብ ዘንድ እንደ ታመነ ዐውቀዋል እንጂ። 8ወደ ተገዘሩ አይሁድ በተላከ ጊዜ ጴጥሮስን የረዳው እርሱ እኔንም ባልተገዘሩ አሕዛብ ዘንድ ረዳኝ። 9የሰጠኝንም ጸጋ ዐውቀው አዕማድ የሚሏቸው ያዕቆብና ኬፋ፥ ዮሐንስም እኛ ወደ አሕዛብ፥ እነርሱም ወደ አይሁድ እንድንሄድ ለእኔና ለበርናባስ ቀኝ እጃቸውን ሰጡን። 10ይልቁንም ነዳያንን እንድናስባቸው ነው፤ ስለዚህም ይህን ነገር ልፈጽመው ተጋሁ።
ጳውሎስ ጴጥሮስን ስለ መቃወሙ
11ነገር ግን ኬፋ ወደ አንጾኪያ በመጣ ጊዜ ፊት ለፊት ተቃወምሁት፤ ነቅፈውት ነበርና። 12ሰዎች ከያዕቆብ ዘንድ ከመምጣታቸው በፊት፥ ከአረማውያን ጋር ይበላ ነበርና፥ በመጡ ጊዜ ግን ተለያቸው፤ ከአይሁድ ወገን የሆኑትን ፈርቶአልና። 13ከአይሁድ ወገንም ወደዚህ ግብር የተመለሱ ብዙዎች ነበሩ፤ በርናባስም እንኳ በግብዝነታቸው ተባበረ። 14ነገር ግን ወደ እውነተኛው ወንጌል እግራቸውን እንዳላቀኑ ባየሁ ጊዜ፥ በሰው ሁሉ ፊት ኬፋን እንዲህ አልሁት፥ “አንተ አይሁዳዊ ስትሆን በአይሁድ ሥርዐት ያይደለ፥ በአረማውያን ሥርዐት የምትኖር ከሆነ እንግዲህ አይሁድ እንዲሆኑ አረማውያንን ለምን ታስገድዳቸዋለህ?” 15እኛ በትውልዳችን አይሁድ ነን፤ ኀጢአተኞች የሆኑ አሕዛብም አይደለንም። 16ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን እንጂ የኦሪትን ሥራ በመሥራት እንደማይጸድቅ እናውቃለንና፤ እኛም የኦሪትን ሥራ በመሥራት ሳይሆን በእርሱ በማመናችን እንጸድቅ ዘንድ በኢየሱስ ክርስቶስ አምነናል፤ ሰው ሁሉ በኦሪት ሥራ አይጸድቅምና። 17በክርስቶስ ልንጸድቅ የምንሻ እኛ እንደ ኀጢአተኞች ከሆን እንግዲህ ክርስቶስ የኀጢአት አገልጋይ መሆኑ ነውን? አይደለም። 18ያን ያፈረስሁትን መልሼ የማንጽ ከሆነ ራሴን ሕግ አፍራሽ አደረግሁ። 19እኔስ ለእግዚአብሔር ሕያው ሆኜ በሁለተኛው ሕግ እኖር ዘንድ ከቀደመው ሕግ ተለየሁ። 20ከክርስቶስ ጋርም ተሰቀልሁ፤ ሕይወቴም አለቀች፤ ነገር ግን በክርስቶስ ሕይወት አለሁ፤ ዛሬም በሥጋዬ የምኖረውን ኑሮ የወደደኝን ስለ እኔም ራሱን አሳልፎ የሰጠውን የእግዚአብሔርን ልጅ በማመን እኖራለሁ። 21የእግዚአብሔርንም ጸጋ አልክድም፤ የኦሪትን ሥራ በመሥራት የሚጸድቁ ከሆነ እንኪያስ ክርስቶስ በከንቱ ሞተ።