የሙሴ መሞትና መቀበር
1ሙሴም ከሞዓብ ሜዳ በኢያሪኮ ፊት ለፊት ወዳለው ወደ ናባው ተራራ ወደ ፈስጋ ራስ ወጣ፤ እግዚአብሔርም እስከ ዳን ድረስ ያለውን የገለዓድን ምድር አሳየው፤ 2የንፍታሌምንም ምድር ሁሉ፥ የምናሴንም ምድር ሁሉ፥ እስከ ምዕራብም ባሕር ድረስ ያለውን የይሁዳን ምድር ሁሉ፤ 3ምድረ በዳውን፥ የኢያሪኮን ዙሪያ፥ እስከ ሴይር ዙሪያ ያለውንም የፊንቆንን ከተማ አሳየው፤ 4እግዚአብሔርም ሙሴን፥ “ለዘርህ እሰጣታለሁ ብዬ ለአብርሃምና ለይስሐቅ ለያዕቆብም የማልሁላቸው ምድር ይህች ናት፤ እነሆም፥ በዐይንህ እንድታያት አደረግሁህ፤ ነገር ግን ወደዚያች አትገባም” አለው። 5የእግዚአብሔር አገልጋይ ሙሴም እንደ እግዚአብሔር ቃል በዚያ በሞዓብ ምድር ሞተ። 6በቤተ ፌጎርም አቅራቢያ በናባው ምድር ቀበሩት፤ እስከ ዛሬም ድረስ መቃብሩን ማንም የሚያውቅ የለም። 7ሙሴም በሞተ ጊዜ ዕድሜዉ መቶ ሃያ ዓመት ነበረ፤ ዐይኖቹም አልፈዘዙም፤ ጕልበቱም አልደከመም ነበር። 8የእስራኤልም ልጆች በዮርዳኖስ በኢያሪኮ አቅራቢያ በሞዓብ ሜዳ ሠላሳ ቀን ለሙሴ አለቀሱለት፤ ለሙሴም ያለቀሱለት የልቅሶው ወራት ተፈጸመ። 9ሙሴም እጆቹን ስለ ጫነበት የነዌ ልጅ ኢያሱ የጥበብን መንፈስ ተሞላ፤ የእስራኤልም ልጆች ታዘዙለት፤ እግዚአብሔርም ሙሴን እንዳዘዘው አደረጉ። 10እግዚአብሔር ፊት ለፊት እንደ ተናገረው እንደ ሙሴ ያለ ነቢይ ከዚያ ወዲህ በእስራኤል ዘንድ አልተነሣም፤ 11በግብፅ ምድር በፈርዖንና በሹሞቹ ሁሉ ላይ፥ በምድሪቱም ሁሉ ላይ ምልክትንና ድንቅን ያደርግ ዘንድ እግዚአብሔር እንደ ላከው ያለ፥ 12በእስራኤል ሁሉ ፊት በታላቅ ተአምር ሁሉና በጸናች እጅ፥ በተዘረጋችም ክንድ ሁሉ እንዳደረገው እንደ ሙሴ ያለ ነቢይ አልተነሣም።