1ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 15
የተማሩትን ስለ ማስታወስ
1ወንድሞቻችን ሆይ፥ ያስተማርኋችሁንና የተቀበላችሁትን ያላችሁበትን፥ በእርሱም የምትድኑበትን ወንጌል አሳስባችኋለሁ። 2ያስተማርኋችሁን ታስቡ እንደ ሆነ በቃሌ አስተምሬአችኋለሁ፤ ያለዚያ ግን ማመናችሁ ከንቱ ነው።
ስለ ጌታችን ትንሣኤና መገለጥ
3እኔ የተማርሁትን አስቀድሜ መጽሐፍ እንደሚል እንዲህ ብዬ አስተማርኋችሁ፥ “ክርስቶስ ስለ ኀጢአታችን ሞተ። 4ተቀበረ፤ እንደ ተጻፈም በሦስተኛው ቀን ተነሣ።” 5ለጴጥሮስ ታየው፤ ከዚህም በኋላ ለዐሥራ አንዱ ደቀ መዛሙርቱ ታያቸው። 6ከዚህም በኋላ ከአምስት መቶ ለሚበዙ ወንድሞች በአንድ ጊዜ ታያቸው፤ ከእነርሱ ብዙዎቹ እስከ ዛሬ አሉ፤ አንዳንዶቹ ግን አንቀላፍተዋል። 7ከዚህም በኋላ ለያዕቆብ ታየው፤ ኋላም ለሐዋርያት ሁሉ፤ 8ከሁሉም በኋላ ጭንጋፍ ለምመስል ለእኔ ታየኝ። 9ከሐዋርያት ሁሉ እኔ አንሣለሁና፤ የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስለ አሳደድሁ ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ የማይገባኝ፥ 10ነገር ግን በእግዚአብሔር ጸጋ አሁን እኔ ባለሁበት አለሁ፤ ለእኔም የሰጠኝ ጸጋው ለከንቱ የሆነብኝ አይደለም፤ እኔም ከሁሉ ይልቅ ደከምሁ፤ ነገር ግን በእኔ ላይ ያደረው የእግዚአብሔር ጸጋ አጸናኝ እንጂ እኔ አይደለሁም። 11አሁንም እኔም ብሆን፥ እነርሱም ቢሆኑ እንዲህ እናስተምራለን፤ እናንተም እንዲሁ አምናችኋል።
ስለ ሙታን መነሣት
12ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቶአል ብለን ለሌላው የምናስተምር ከሆነ፥ እንግዲህ ከመካከላችሁ ሙታን አይነሡም የሚሉ እንዴት ይኖራሉ? 13ሙታን የማይነሡ ከሆነ ክርስቶስም ከሙታን ተለይቶ አልተነሣማ፤ 14ክርስቶስም ከሙታን ካልተነሣ እንግዲያስ ትምህርታችን ከንቱ ነው፤ የእናንተም እምነታችሁ ከንቱ ነው። 15እኛም በእግዚአብሔር ላይ የሐሰት ምስክሮች ሆነናል፤ ክርስቶስን አስነሣው ብለናልና፥ እንግዲያ ሳያስነሣው ነውን?። 16ሙታን የማይነሡ ከሆነ ክርስቶስም ከሙታን አልተነሣማ። 17ክርስቶስም ከሙታን ካልተነሣ ማመናችሁ ከንቱ ነው፤ ገናም በኀጢአታችሁ አላችሁ። 18እንግዲያስ በክርስቶስ አምነው የሞቱ ጠፍተዋላ። 19በዚህ ዓለም ሕይወት ብቻ ክርስቶስን ተስፋ ከአደረግነው ከሰው ሁሉ ይልቅ ጉዳተኞች ነን። 20አሁንም ክርስቶስ ከሞቱ ሰዎች ሁሉ አስቀድሞ ተነሥቶአል። 21በመጀመሪያው ሰው ሞት መጥቶአልና፤ በሁለተኛው ሰው ትንሣኤ ሙታን ሆነ። 22ሁሉ በአዳም እንደሚሞት እንዲሁ በክርስቶስ ሁሉ ሕያዋን ይሆናሉ። 23ነገር ግን ሰው ሁሉ በየሥርዐቱ ይነሣል፤ በመጀመሪያ ከሙታን የተነሣ ክርስቶስ ነው፤ ከዚያ በኋላ በክርስቶስ ያመኑ እርሱ በሚመጣበት ጊዜ ይነሣሉ። 24እግዚአብሔር አብ መንግሥቱን እጅ ባደረገ ጊዜ፥ ገዥም ሁሉ፥ ንጉሥም ሁሉ፥ ኀይልም ሁሉ በተሻረ ጊዜ፥ ያንጊዜ ፍጻሜ ይሆናል። 25ጠላቶቹ ሁሉ ከእግሩ በታች እስኪወድቁ ድረስ ይነግሥ ዘንድ አለውና። 26ከዚያ በኋላ የመጨረሻው ጠላት ይሻራል፤ ይኸውም ሞት ነው። 27ሁሉን ከእግሩ በታች አስገዝቶለታልና፥ “ሁሉ ይገዛለት” ባለ ጊዜ ግን ሁሉን ከሚያስገዛለት በቀር እንደ ሆነ የታወቀ ነው። 28ሁሉም በተገዛለት ጊዜ ግን እግዚአብሔር በሁሉ ቦታ በሁሉ ይሆን ዘንድ፥ ያን ዕለት ወልድም ሁሉን ላስገዛለት ይገዛል። 29ያለዚያማ ለምን ያጠምቃሉ? ሙታን እንዲነሡ አይደለምን? ሙታን የማይነሡ ከሆነስ ለምን ያጠምቃሉ? 30እንግዲህ እኛስ ሁልጊዜ መከራን ስለምን እንቀበላለን? 31ወንድሞቻችን ሆይ፥ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በሆነውና በእናንተ ላይ ባለኝ ትምክህት ሁልጊዜ እገደላለሁ። 32በውኑ በኤፌሶን ከአውሬ ጋር የታገልሁ ለሰው ብዬ ነውን? ምንስ ይጠቅመኛል? ሙታን የማይነሡ ከሆነ እንግዲህ እንብላ እንጠጣ፥ ነገም እንሞታለን። 33ወንድሞቻችን አያስቱአችሁ፤ ክፉ ነገር መልካም ጠባይን ያበላሻልና።
ስለ ትንሣኤ በምሳሌ ትምህርት
34ለጽድቅ ትጉ፤ አትሳቱ፤ እግዚአብሔርን የማያውቁት ሰዎች አሉና፤ ነገር ግን እንድታፍሩ ይህን እላችኋለሁ፤ 35ሙታን እንዴት ይነሣሉ? የሚነሡስ በምን አካላቸው ነው? የሚል አለ። 36አንተ ሰነፍ! አንተ የምትዘራው እንኳን ካልፈረሰ አይበቅልም። 37የምትዘራውም የስንዴ ቢሆን፥ የሌላም ቢሆን የምትዘራት ቅንጣት ብቻ ናት እንጂ ይህ ኋላ የሚገኘው አገዳው አይደለም። 38እግዚአብሔር ግን እንደ ወደደ አገዳን ይሰጠዋል፤ ለእያንዳንዱ ዘርም አገዳው እየራሱ ነው። 39የፍጥረቱ ሁሉ አካል አንድ አይደለምና፤ የሰው አካል ሌላ ነው፤ የእንስሳም አካል ሌላ ነው፤ የወፍ አካልም ሌላ ነው፤ የዓሣ አካልም ሌላ ነው። 40ሰማያዊ አካል አለ፤ ምድራዊ አካልም አለ፤ ነገር ግን በሰማይ ያለው አካል ክብሩ ልዩ ነው፤ በምድርም ያለው አካል ክብሩ ልዩ ነው። 41የፀሐይ ክብሩ ሌላ ነው፤ የጨረቃም ክብሩ ሌላ ነው፤ የከዋክብትም ክብራቸው ሌላ ነው፤ ኮከብ ከኮከብ በክብር ይበልጣልና። 42የሙታን ትንሣኤያቸው እንዲሁ ነው፥ በሚፈርስ አካል ይዘራል፤ በማይፈርስ አካል ይነሣል። 43በውርደት ይዘራል፤ በክብር ይነሣል፤ በድካም ይዘራል፤ በኀይል ይነሣል። 44ሥጋዊ አካል ይዘራል፤ መንፈሳዊ አካል ይነሣል፤ ሥጋዊ አካል አለና መንፈሳዊ አካልም ደግሞ አለ። 45መጽሐፍ እንዲሁ ብሎአልና የመጀመሪያው ሰው አዳም በነፍስ ሕያው ሆኖ ተፈጠረ፤ ሁለተኛው አዳም ግን ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ነው። 46ነገር ግን አስቀድሞ ሥጋዊው፥ ቀጥሎም መንፈሳዊው ነው እንጂ፥ መንፈሳዊው መጀመሪያው አይደለም። 47መጀመሪያው ሰው ከመሬት የተገኘ መሬታዊ ነው፤ ሁለተኛው ሰው ከሰማይ የወረደ ሰማያዊ ነው። 48መሬታውያኑ እንደዚያ እንደ መሬታዊው ናቸው፤ ሰማያውያኑም እንደዚያ እንደ ሰማያዊው ናቸው። 49የመሬታዊውን መልክ እንደ ለበስን እንዲሁ የሰማያዊውን መልክ ደግሞ እንለብሳለን። 50ወንድሞቻችን ሆይ፥ ይህን እንነግራችኋለን፦ ሥጋዊና ደማዊ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርስም፥ የሚፈርሰው የማይፈርሰውን አይወርስም። 51እነሆ፥ አንድ ምሥጢርን እነግራችኋለሁ፥ ሁላችን የምንሞት አይደለም። 52ነገር ግን የኋለኛው መለከት ሲነፋ ሁላችን እንደ ዐይን ጥቅሻ በአንድ ጊዜ እንለወጣለን፤ መለከት ይነፋል፤ ሙታንም የማይፈርሱ ሁነው ይነሣሉ፤ እኛም እንለወጣለን። 53ይህ የሚፈርሰው የማይፈርሰውን፥ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ይለብስ ዘንድ አለውና። 54ይህ የሚፈርሰው የማይፈርሰውን በለበሰ ጊዜ፥ የሚሞተውም የማይሞተውን በለበሰ ጊዜ፤ “ሞት በመሸነፍ ተዋጠ” ተብሎ የተጻፈው ያንጊዜ ይፈጸማል። 55“ሞት ሆይ፥ እንግዲህ መውጊያህ ወዴት አለ? መቃብር ሆይ፥ አሸናፊነትህ ወዴት አለ?” 56የሞት መውጊያ ኀጢአት ናት፥ የኀጢአትም ኀይልዋ ኦሪት ናት። 57በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ድል መንሣትን ለሰጠን ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን። 58አሁንም የተወደዳችሁ ወንድሞቻችን ሆይ፥ የጸናችሁና የማትናወጡ ሁኑ፤ ዘወትር በጎ ምግባርን አብዝታችሁ ለእግዚአብሔር አበርክቱ፤ ስለ ጌታችን መድከማችሁ ለከንቱ እንዳይደለ ታውቃላችሁና።