ባልንጀራን ስለ ማጽናናት
1እምነቱ ደካማ የሆነውን ሰው ታገሡት፤ በዐሳቡም አትፍረዱ። 2ሁሉን ይበላ ዘንድ እንደ ተፈቀደለት የሚያምን ሁሉን ይብላ፤ የሚጠራጠር ግን አትክልት ይብላ። 3የሚበላውም የማይበላውን አይናቀው፤ የማይበላውም የሚበላውን አይንቀፈው፤ ሁሉንም እግዚአብሔር አውቆአቸዋልና። 4እንግዲህ የሌላውን ሎሌ የምትነቅፍ አንተ ማነህ? እርሱ ቢቆም ወይም ቢወድቅ ለጌታው ነው። ነገር ግን እግዚአብሔር ሊያነሣው ይችላልና ይቆማል። 5ከቀን ቀን የሚከለከል አለና፤ ዘወትርም የሚከለከል አለና፤ ነገር ግን ሁሉም ልቡ እንደ ወደደ ያድርግ። 6አንዳንድ ቀን የተከለከለም ለእግዚአብሔር ተከለከለ፤ ዘወትር የተከለከለም ለእግዚአብሔር ተከለከለ፤ የበላም ለእግዚአብሔር በላ፤ እግዚአብሔርንም ያመሰግነዋል፤ ያልበላም ለእግዚአብሔር አልበላም፤ እግዚአብሔርንም ያመሰግነዋል። 7ከመካከላችንም ለራሱ የሚኖር፥ ለራሱም የሚሞት የለም። 8በሕይወት ብንኖርም ለእግዚአብሔር እንኖራለን፤ ብንሞትም ለእግዚአብሔር እንሞታለን፤ እንግዲህ በሕይወት ብንኖርም ብንሞትም ለእግዚአብሔር ነን። 9ስለዚህ ሕያዋንንና ሙታንን ይገዛ ዘንድ ክርስቶስ ሞተ፥ ተነሣም። 10እንግዲህ በወንድምህ ላይ የምትፈርድ አንተ ምንድን ነህ? ወንድምህንስ የምትነቅፍ አንተ ምንድን ነህ? ሁላችን በክርስቶስ የፍርድ ዙፋን ፊት እንቆማለንና። 11እግዚአብሔር እንዲህ ብሎአልና፥ “እኔ ሕያው ነኝ፤ ጕልበትም ሁሉ ለእኔ ይሰግዳል፤ አንደበትም ሁሉ ለእኔ ይገዛል።” 12እነሆ፥ ሁላችን በእግዚአብሔር ዘንድ እንደምንመረመር ታወቀ።
ለባልንጀራ ዕንቅፋት ስላለመሆን
13እንግዲህ ከዛሬ ጀምሮ እርስ በርሳችን አንነቃቀፍ፤ ይልቁንም ለወንድም እንቅፋትን ወይም ማሰናከያን ማንም እንዳያኖር ይህን ዐስቡ። 14በራሱ ርኩስ የሆነ ነገር እንደሌለ በጌታችን በኢየሱስ ሆኜ ዐውቄአለሁ፤ ተረድቼአለሁም፤ ነገር ግን ማናቸውም ነገር ርኩስ እንደሚሆን ለሚያስብ ያ ለእርሱ ርኩስ ነው። 15በመብል ምክንያት ባልንጀራህን የምታሳዝን ከሆንህ ፍቅር የለህም፤ በውኑ ክርስቶስ ስለ እርሱ የሞተለት ያ ሰው በመብል ምክንያት ሊጐዳ ይገባልን? 16እንግዲህ ጌታችን የሰጠንን መልካሙን ነገር አታሰድቡ። 17የእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም፤ በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ ነው እንጂ መብልና መጠጥ አይደለምና። 18እንዲህ አድርጎ ለክርስቶስ የሚገዛ ግን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና በሰውም ዘንድ የተመረጠ ነው። 19አሁንም ወንድማችን ይታነጽ ዘንድ ሰላምን እንከተላት። 20በመብል ምክንያት የእግዚአብሔርን ፍጥረት አናፍርስ፤ ለንጹሓን ሁሉ ንጹሕ ነው፤ ለሰውስ ክፉው ነገር በመጠራጠር መብላት ነው። 21ለወንድም ዕንቅፋት ከመሆን ሥጋን አለመብላት ወይንንም አለመጠጣት ይሻላል። 22እምነት ካለህ በእግዚአብሔር ፊት ባመንኸው እምነት ራስህን አጽና፤ ባገኘው አእምሮም ራሱን የሚዘልፍ ብፁዕ ነው። 23የሚጠራጠር ግን ቢበላ ይፈረድበታል፤ በማመን አልሆነምና፤ ያለ እምነትም የሚደረግ ሁሉ ኀጢአትና በደል ነው።