በክርስቶስ ሐዲስ ሕይወት
1ወንድሞቻችን፥ ሰውነታችሁን ለእግዚአብሔር ሕያውና ቅዱስ፥ ደስ የሚያሰኝም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እማልዳችኋለሁ። ይህም በዕውቀት የሚሆን አገልግሎታችሁ ነው። 2ይህን ዓለም አትምሰሉ፤ ልባችሁንም አድሱ፤ እግዚአብሔር የሚወደውን መልካሙንና እውነቱን፥ ፍጹሙንም መርምሩ። 3በተሰጠኝ በእግዚአብሔር ጸጋ ሁላችሁም እንዳትታበዩ እነግራችኋለሁ፤ ራሳችሁን ከዝሙት የምታነጹበትን ዐስቡ እንጂ ትዕቢትን አታስቡ፤ ሁሉም እንደ እምነቱ መጠን እግዚአብሔር እንደ አደለው ይኑር። 4በአንዱ ሰውነታችን ብዙ የአካል ክፍሎች እንዳሉ፥ ሥራቸውም ልዩ ልዩ እንደ ሆነ፥ 5እንዲሁ ሁላችን ብዙዎች ስንሆን በክርስቶስ አንድ አካል ነን፤ እርስ በርሳችንም እያንዳንዳችን የሌላው አካሎች ነን፤ ስጦታውም ልዩ ልዩ ነው፤ 6እግዚአብሔርም በሰጠን ጸጋ መጠን ልዩ ልዩ ስጦታ አለን። ትንቢት የሚናገር እንደ እምነቱ መጠን ይናገር። 7የሚያገለግልም በማገልገሉ ይትጋ፤ የሚያስተምርም በማስተማሩ ይትጋ፤ 8የሚመክርም በመምከሩ ይትጋ፤ የሚሰጥም በልግስና ይስጥ፤ የሚገዛም በትጋት ይግዛ፤ የሚመጸውትም በደስታ ይመጽውት።
ስለ ልዩ ልዩ በጎ ምግባር
9ፍቅራችሁ ያለ ግብዝነት ይሁን፤ ከክፉ ራቁ፤ በጎውንም ያዙ፤ ለጽድቅ አድሉ፤ 10እርስ በርሳችሁ በወንድማማችነት መዋደድ ተዋደዱ፤ የምትራሩም ሁኑ፤ እርስ በርሳችሁ ተከባበሩ፤ መምህሮቻችሁንም አክብሩ። 11ለሥራ ከመትጋት አትስነፉ፤ በመንፈስ ሕያዋን ሁኑ፤ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ 12በተስፋ ደስ ይበላችሁ፤ በመከራ ታገሡ፤ ለጸሎት ትጉ። 13በችግራቸው ቅዱሳንን ለመርዳት ተባበሩ፤ እንግዳ መቀበልንም አዘውትሩ። 14የሚያሳድዱአችሁን መርቁ፤ መርቁ እንጂ አትርገሙ። 15ደስ ከሚለው ጋር ደስ ይበላችሁ፤ ከሚያለቅሰው ጋርም አልቅሱ። 16እርስ በርሳችሁም በአንድ ዐሳብ ተስማሙ፤ ትዕቢትን ግን አታስቡ፤ ራሱን የሚያዋርደውንም ሰው ምሰሉ፤ እና ዐዋቆች ነን አትበሉ። 17ክፉ ላደረገባችሁም ክፉ አትመልሱለት፤ በሰው ሁሉ ፊት በጎውን ተነጋገሩ። 18ቢቻላችሁስ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ። 19ወንድሞቻችን፥ ራሳችሁ አትበቀሉ፤ ቍጣን አሳልፏት፥ “እኔ እበቀላለሁ፤ እኔ ብድራትን እከፍላለሁ ይላል እግዚአብሔር” ተብሎ ተጽፎአልና። 20ጠላትህ ቢራብ አብላው፤ ቢጠማም አጠጣው፤ ይህን ብታደርግ የእሳት ፍሕም በራሱ ላይ ትከምራለህ። 21ክፉውን በመልካም ሥራ ድል ንሣው እንጂ ክፉውን በክፉ ድል አትንሣው።