የባቢሎን ውድቀት
1አንቺ ድንግል የባቢሎን ልጅ ሆይ፥ ውረጂ፤ በትቢያም ላይ ተቀመጪ፤ የከለዳውያን ሴት ልጅ ሆይ፥ ከዚህ በኋላ ለስላሳና ቅምጥል አትባዪምና ያለ ዙፋን በመሬት ላይ ተቀመጪ። 2ወፍጮ ወስደሽ ዱቄትን ፍጪ፤ ክንብንብሽን ግለጪ፤ ሽበትሽ ይታይ፤ ባትሽን ግለጪ፤ ወንዙንም ተሻገሪ። 3ኀፍረትሽ ይገለጣል፤ ውርደትሽም ይታያል፤ ጽድቅ ከአንቺ ይወሰዳል፤ እንዲሁም በአንቺ ፋንታ ሰውን አሳልፌ አልሰጥም። 4ታዳጊሽ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፥ ስሙ የእስራኤል ቅዱስ ነው። 5የከለዳውያን ሴት ልጅ ሆይ፥ ከዚህ በኋላ፥ “የመንግሥታት እመቤት” አትባዪምና በድንጋጤ ዝም ብለሽ ተቀመጪ፤ ወደ ጨለማም ውስጥ ግቢ። 6በሕዝቤ ላይ ተቈጥቼ ነበር፤ ርስቴንም አረከስሽ፤ በእጅሽም አሳልፌ ሰጠኋቸው፤ ለሽማግሌዎቻቸው አልራራሽም፤ ቀንበራቸውንም እጅግ አክብደሻል። 7አንቺም፥ “እኔ ለዘለዓለም እመቤት እሆናለሁ” ብለሻል፤ ይህንም በልብሽ አላሰብሽም፤ ፍጻሜውንም አላስታወስሽም። 8አሁንም አንቺ ቅምጥል ተዘልለሽ የምትቀመጪ፥ በልብሽም፥ “እኔ ነኝ ከእኔም በቀር ሌላ የለም፤ መበለትም ሆኜ አልኖርም፤ የወላድ መካንነትንም አላውቅም” የምትዪ፥ ይህን ስሚ፤ 9አሁን ግን በአንድ ቀን እነዚህ ሁለት ነገሮች በድንገት ይመጡብሻል፤ የወላድ መካንነትና መበለትነት ስለ መተቶችሽ ብዛትና ስለ አስማቶችሽ ጽናት ፈጽመው ይመጡብሻል። 10በክፋትሽ ታምነሻል፤ አንቺ ግን፥ “እኔ ነኝ፤ ከእኔ በቀር ሌላ የለም” ብለሻል፤ በዝሙትሽ ኀፍረት ያሰብሽውንም ዕወቂ፤ በልብሽ፥ “እኔ ነኝ ከእኔም በቀር ሌላ የለም” ብለሻልና። 11ስለዚህ ምክንያት ጥፋት ይመጣብሻል፤ ጥልቀቱን አታውቂም፤ በውስጡም ትወድቂያለሽ፤ ጕስቁልና ይመጣብሻል፤ ማምለጥም አይቻልሽም፤ ሞት ድንገት ይመጣብሻል፤ አታውቂምም። 12ምናልባትም ሊያድንሽ የሚችል እንደ አለ፥ ከአስማቶችሽና ከሕፃንነትሽ ጀምረሽ ከተማርሽው ከመተቶችሽ ብዛት ጋር ቁሚ። 13በክፉ ምክርሽ ደክመሻል፤ አሁንም የሰማይን ከዋክብት የሚቈጥሩ፥ ከዋክብትንም የሚመለከቱ ይነሡ፤ ያድኑሽም፤ ምን እንደሚመጣብሽም ይንገሩሽ፤ 14እነሆ፥ ሁሉም እንደ እብቅ እሳት ይቃጠላሉ፤ ሰውነታቸውንም ከነበልባል ኀይል አያድኑም፤ እንደ እሳትም ፍም ይሆኑብሻል፤ በላያቸውም ትቀመጫለሽ። 15እነርሱ ረዳቶችሽ ይሆናሉ፤ ከሕፃንነትሽ ጀምረሽ ደከምሽ፤ ሰው በራሱ ይሳሳታል፤ ለአንቺ ግን መድኀኒት የለሽም።