እግዚአብሔር ሕዝቡን እንደሚወድድ
1እስራኤል ሕፃን በነበረ ጊዜ ወደድሁት፤ ልጄንም ከግብፅ ጠራሁት፤ 2አብዝች ብጠራቸው አጥብቀው ከፊቴ ራቁ፤ ለበዓሊምም ይሠዉ ነበር፤ ለተቀረጹ ምስሎችም ያጥኑ ነበር። 3እኔም ኤፍሬምን ወደድሁት፤ በክንዴም ተቀበልሁት፤ እኔም እፈውሳቸው እንደ ነበርሁ አላወቁም። 4በሰው ገመድ በፍቅርም እስራት ሳብኋቸው፤ ለእነርሱም ፊቱን በጥፊ እንደሚመቱት ሰው ሆንሁላቸው፤ ወደ እርሱም እመለከታለሁ፤ እችለውማለሁ። 5ኤፍሬም በግብፅ ተቀመጠ፤ አሦርም ንጉሡ ነው፤ መመለስን እንቢ ብሎአልና። 6ጦር በከተማው ደከመች፤ ከእጁም ይለያታል፤ ከሥራቸውም ፍሬ ይበላሉ። 7ሕዝቤም ከመኖሪያው ተነሥቶአል፤ እግዚአብሔርም በክብሩ ላይ ተቈጣ፤ ከፍ ከፍም አያደርገውም። 8እኔም “አምልኮቴን ትተሃል አልሁ፤ ኤፍሬም ሆይ! እንዴት አደርግሃለሁ? እስራኤል ሆይ! እንዴትስ እደግፍሃለሁ? እንዴትስ አደርግሃለሁ? እንደ አዳማ ነውን? ወይስ እንደ ሲባዮ? ልቤ በውስጤ ተናውጣለች፤ ምሕረቴም ተገልጣለች። 9እኔ አምላክ ነኝ እንጂ ሰው አይደለሁምና፥ በመካካልህም ቅዱሱ ነኝና እንግዲህ የቍጣዬን መቅሠፍት አላደርግም፤ ኤፍሬምንም ያጠፉት ዘንድ አልተውም፤ ወደ ከተማም አልገባም አልሁ። 10ጌታ እግዚአብሔርን እከተለው ዘንድ እሄዳለሁ፤ እርሱ ያድነናልና፤ እርሱም እንደ አንበሳ ያገሣል፤ የውኃ ልጆችም ይደነግጣሉ። 11እንደ ወፍ ከግብፅ፥ እንደ ርግብም ከአሶር ምድር እየተንቀጠቀጡ ይወጣሉ፤ ወደ ቤታቸውም እመልሳቸዋለሁ፥” ይላል እግዚአብሔር።