ስለ ካህኑ መልከ ጼዴቅ
1የሳሌም ንጉሥ፥ የልዑል እግዚአብሔርም ካህን የሆነ፥ ይህ መልከ ጼዴቅ፥ አብርሃም ነገሥታትን ድል ነሥቶ በተመለሰ ጊዜ ከእርሱ ጋር ተገናኝቶ ባረከው። 2አብርሃምም ከገንዘቡ ሁሉ ከዐሥር አንድ ሰጠው፤ መጀመሪያ የስሙ ትርጓሜ የጽድቅ ንጉሥ ነበር፤ በኋላም የሳሌም ንጉሥ ተባለ፤ የሰላም ንጉሥ ማለት ነው። 3አባት የለውም፤ እናትም የለችውም፤ ትውልዱም አይታወቅም፤ ለዘመኑ መጀመሪያ፥ ለሕይወቱም መጨረሻ የለውም፤ ክህነቱ የወልደ እግዚአብሔር ምሳሌ ሆኖ ለዘለዓለም ይኖራል። 4የአባቶች አለቃ አብርሃም ከምርኮው ሁሉ የሚሻለውን ዐሥራት የሰጠውን የዚህን ካህን ክብር ታያላችሁን? 5ከሌዊ ልጆችም፥ ክህነትን የሚቀበሉት ከሕዝቡ ማለት ከወንድሞቻቸው፥ እነርሱ ምንም ከአብርሃም ወገብ ቢወጡ ከእነርሱ ዐሥራትን በሕግ እንዲያስወጡ ትእዛዝ አላቸው። 6ወገናቸው ላይደለ ለእርሱ ግን አብርሃም ዐሥራትን ሰጠው፤ እርሱም ተስፋ ያለው አብርሃምን ባረከው። 7ነገር ግን ታላቁ ታናሹን እንደሚባርከው ያለ ጥርጥር ይታወቃል። 8በዚህስ የሚሞት ሰው ዐሥራትን ይቀበላል፤ በወዲያው ግን ሕያው እንደ ሆነ መጽሐፍ የሚመሰክርለት እርሱ ይቀበላል። 9እንደ ተነገረም ዐሥራትን የሚቀበል ሌዊ ስንኳን በአብርሃም በኩል ዐሥራትን ሰጠ። 10መልከ ጼዴቅ በተገናኘው ጊዜ ገና በአባቱ በአብርሃም ወገብ ነበርና። 11እንግዲህ ሕዝቡ በሌዊ ክህነት የተመሠረተን ሕግ ተቀብለዋልና በዚያ ክህነት ፍጹምነት የተገኘ ቢሆን፥ እንደ አሮን ሹመት የማይቈጠር፥ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ግን የሆነ ሌላ ካህን ሊነሣ ወደ ፊት ስለምን ያስፈልጋል? 12ክህነታቸው ታልፍ ዘንድ አላትና፤ ክህነታቸው ካለፈችም ኦሪታቸው ታልፋለች። 13ይህ ነገር የተነገረለት እርሱ በሌላ ወገን ተካፍሎአልና፥ ከዚያም መሠዊያውን ያገለገለ ማንም የለም። 14ጌታችን ከይሁዳ ነገድ እንደ ወጣ የተገለጠ ነውና፤ ስለዚህም ነገድ ሙሴ ምንም እንኳን ስለ ክህነት አልተናገረም። 15ይልቁንም ይህ እጅግ ያስረዳል፤ በመልከ ጼዴቅ ክህነት አምሳል ሌላ ካህን ይነሣል ብሎአልና። 16ይኸውም በማያልፍ ሕይወት ኀይል እንጂ ለሥጋና ለደም በተሠራ ሕግ አይደለም። 17“እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት የዘለዓለም ካህን አንተ ነህ” ብሎ ይመሰክራልና። 18ስለዚህም የምትደክም፥ የማትጠቅምም ስለ ሆነች የቀደመችው ትእዛዝ ተሽራለች። 19ኦሪት ምንም ግዳጅ አልፈጸመችምና፤ ነገር ግን በእርስዋ ፋንታ ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት ከእርስዋ የሚሻል ተስፋ ገብቶአል። 20እርሱ ያለ መሐላ አልሆነም፤ ያለ መሐላ የተሾሙ ካህናት አሉና። 21በመሐላ የሾመውን ግን፥ “እግዚአብሔር ማለ፥ አይጸጸትምም፤ አንተ እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት የዘለዓለም ካህን ነህ” አለው። 22ኢየሱስ ይህን ያህል በምትበልጥና ከፍ ባለች ሹመት ተሾመ። 23ለእነዚያስ ብዙዎች ካህናት ነበሩአቸው፤ ሞት ይሽራቸው፥ እንዲኖሩም አያሰናበታቸውም ነበርና። 24እርሱ ግን ለዘለዓለም ይኖራል፤ ክህነቱ አይሻርምና። 25ዘወትር በእርሱ በኩል ወደ እግዚአብሔር የሚቀርቡትን ሊያድናቸው ይቻለዋል፤ ለዘለዓለምም ሕያው ነውና ያስታርቃቸዋል። 26ቅዱስና ያለ ተንኰል፥ ነውርም የሌለበት፥ ከኀጢአተኞችም የተለየ፥ ከሰማያትም ከፍ ከፍ ያለ፥ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባናል። 27እርሱም እንደ እነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኀጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኀጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጎአልና። 28ኦሪትስ የሚሞት ሰውን ሊቀ ካህናት አድርጋ ትሾማለች፤ ከኦሪት በኋላ የመጣው የእግዚአብሔር የመሐላ ቃሉ ግን ዘለዓለም የማይለወጥ ፍጹም ወልድን ካህን አድርጎ ሾመልን።