የሥጋዌ ምሥጢር
1ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዐይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናገረ። 2በኋላ ዘመን ግን ሁሉን ወራሽ ባደረገው፥ ሁሉንም በፈጠረበት በልጁ ነገረን። 3እርሱም የክብሩ መንጸባረቅና የመልኩ ምሳሌ ሆኖ፥ ሁሉን በሥልጣኑ ቃል እየደገፈ ኀጢአታችንን በራሱ ካነጻ በኋላ፥ በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀመጠ። 4በዚህን ያህል መብለጥ ከመላእክት በላይ ሆኖ ከስማቸው የሚበልጥና የሚከብር ስምን ወረሰ። 5ከመላእክትስ ከሆነ ጀምሮ፥ “አንተ ልጄ ነህ፥ እኔ ዛሬ ወለድሁህ” ዳግመኛም፥ “እኔ አባት እሆነዋለሁ እርሱም ልጄ ይሆነኛል” ያለው ከቶ ለማን ነው? 6ዳግመኛም በኵርን ወደ ዓለም በላከው ጊዜ “የእግዚአብሔር መላእክት ሁሉ ይሰግዱለታል” አለ። 7ስለ መላእክቱም፥ “መላእክቱን ነፋሳት፥ የሚላኩትንም የእሳት ነበልባል የሚያደርጋቸው እርሱ ነው” አለ። 8ስለ ልጁ ግን፥ “ጌታ ሆይ፥ ዙፋንህ ለዘለዓለም ነው፤ የመንግሥትህ በትርም የጽድቅ በትር ነው” አለ። 9“ጽድቅን ወደድህ፤ ዐመፃንም ጠላህ፤ ስለዚህም እግዚአብሔር አምላክህ እንዳንተ ካሉት ይልቅ የሚበልጥ የደስታ ዘይትን ቀባህ።” 10ዳግመኛም እንዲህ አለ፥ “አቤቱ አንተ አስቀድሞ ምድርን መሠረትህ፤ ሰማያትም የእጆችህ ሥራ ናቸው። 11እነርሱ ያልፋሉ፤ አንተ ግን ትኖራለህ፤ ሁሉ እንደ ልብስ ያረጃል፤ 12እንደ መጋረጃም ትጠቀልላቸዋለህ፤ ይለወጣሉም፤ አንተ ግን መቼም መች አንተ ነህ፤ ዘመንህም የማይፈጸም ነው።” 13ከሆነ ጀምሮ ከመላእክት፥ “ጠላቶችህን ከእግርህ ጫማ በታች እስከ አደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ” ማንን አለው? 14መላእክት ሁሉ መናፍስት አይደሉምን? የዘለዓለም ሕይወትን ይወርሱ ዘንድ ስለ አላቸው ሰዎችስ ለአገልግሎት ይላኩ የለምን?