2ኛ ወደ ቆሮንቶስ ሰዎች 6
ምግባርን ስለ ማቅናት
1ከእርሱም ጋር አብረን እየሠራን፥ የተቀበላችኋትን የእግዚአብሔር ጸጋ ለከንቱ እንዳታደርጓት እንማልዳችኋለን። 2እንዲህ ብሎአልና፥ “በተመረጠችው ቀን ሰማሁህ፤ በመዳንም ቀን ረዳሁህ” እነሆ፥ የተመረጠችው ቀን ዛሬ ናት። 3አገልግሎታችንም እንዳይነቀፍ፥ በአንዳች ነገር ማሰናከያ እንዳንሰጥ እንጠንቀቅ። 4ነገር ግን በሁሉ ራሳችንን አቅንተን፥ የእግዚአብሔር አገልጋዮች እንሁን፤ በብዙ ትዕግሥትና በመከራ፥ በችግርና በጭንቀት ሁሉ፥ 5በመገረፍና በመታሰር፥ በድካምና በመታወክ፥ በመትጋትና በመጾም፥ 6በንጽሕናና በዕውቀት፥ በምክርና በመታገሥ፥ በቸርነትና በመንፈስ ቅዱስ፥ አድልዎ በሌለበት ፍቅር፥ 7በእውነት ቃል፥ በእግዚአብሔር ኀይል ለቀኝና ለግራ በሚሆን የጽድቅ የጦር ዕቃ፥ 8በክብርና በውርደት፥ በምርቃትና በርግማን፥ እንደ አሳቾች ስንታይ እውነተኞች ነን። 9እንደማይታወቁ ስንታይ የታወቅን ነን፤ እንደ ሰነፎች ስንታይም ልባሞች ነን፤ እንደ ሙታን ስንታይ ሕያዋን ነን፤ የተቀጣን ስንሆንም አንገደልም። 10ኀዘንተኞች ስንሆን ዘወትር ደስተኞች ነን፤ እንደ ድሆች ስንሆን ብዙዎችን እናበለጽጋለን፤ ምንም የሌለን ስንሆን ሁሉ በእጃችን ነው።
ስለ ቆሮንቶስ ሰዎች
11የቆሮንቶስ ሰዎች ሆይ፥ ለእናንተ አፋችን የተከፈተ ነው፤ ልባችንም የሰፋ ነው። 12ከእናንተ የደረሰ ኀዘን በእኛ የለም፤ ከእኛም በእናንተ ላይ የደረሰ ኀዘን የለም፤ ነገር ግን በልባችሁ አዝናችኋል። 13ልጆች እንደ መሆናችሁ፥ ይህን እላችኋለሁ፤ ከእናንተ ላይ ስለሚገባኝ ብድራቴ እናንተ ፍቅራችሁን አስፉልኝ።
ከማያምኑ ስለ መለየት
14ተጠራጣሪዎች አትሁኑ፤ ወደማያምኑ ሰዎች አንድነትም አትሂዱ፤ ጽድቅን ከኀጢአት ጋር አንድ የሚያደርጋት ማን ነው? ብርሃንንስ ከጨለማ ጋር የሚቀላቅል ማን ነው? 15ክርስቶስን ከቤልሆር ጋር አንድ የሚያደርገው ማን ነው? ወይስ ምእመናንን ከመናፍቃን ጋር አንድ ወገን የሚያደርጋቸው ማን ነው? 16የእግዚአብሔርን ታቦትስ በጣዖት ቤት ውስጥ የሚያኖር ማን ነው? የሕያው እግዚአብሔር ማደሪያዎች እኛ አይደለንምን? እግዚአብሔር እንዲህ ሲል ተናገረ፥ “እኔ በእነርሱ አድራለሁ፤ በመካከላቸውም እኖራለሁ፤ አምላካቸውም እሆናቸዋለሁ፤ እነርሱም ሕዝቤ ይሆኑኛል።” 17ስለዚህም “ከመካከላቸው ተለይታችሁ ውጡ፤ ከእነርሱም ተለዩ፤ ወደ ርኩሳንም አትቅረቡ፥ እኔም እቀበላችኋለሁ። 18አባት እሆናችኋለሁ፤ እናንተም ወንዶችና ሴቶች ልጆች ትሆኑኛላችሁ አለ ሁሉን የሚገዛ እግዚአብሔር።”