የማይገባ ሥራ በሚሠሩ ላይ የሚሰጥ ቅጣት
1በእናንተ ላይ ዝሙት ይሰማል፤ እንደዚህ ያለው ዝሙትም አረማውያን እንኳ የማያደርጉት ነው፤ ያባቱን ሚስት ያገባ አለና። 2እናንተም ከዚህ ጋር ትዕቢተኞች ናችሁ፤ ይልቁንም ይህን ያደረገው ከእናንተ ይለይ ዘንድ ለምን አላዘናችሁበትም? 3እኔ በሥጋዬ ከእናንተ ጋር ባልኖር፥ በመንፈሴ ከእናንተ ጋር አለሁ፤ እነሆ፥ ከእናንተ ጋር እንደ አለሁ ሆኜ፥ ይህን ሥራ የሠራውን እፈርድበታለሁ። 4በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተሰብስባችሁ፥ በእኔ ሥልጣን፥ በጌታችን በኢየሱስም ኀይል፥ 5ሥጋውን ጎድቶ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚመጣበት ቀን ነፍሱ ትድን ዘንድ እንዲህ ያለውን ሰው ለሰይጣን አሳልፋችሁ ስጡት። 6እንግዲያስ መታበያችሁ መልካም አይደለም፤ ጥቂቱ እርሾ ብዙውን ሊጥ እንደሚያመጥ አታውቁምን? 7እንግዲህ ለአዲስ ቡሆ ትሆኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ ከእናንተ አርቁ፤ ገና ቂጣ ናችሁና፤ ፋሲካችን ክርስቶስ ተሠውቶ የለምን? 8አሁንም በዓላችሁን አድርጉ፤ ነገር ግን እውነትና ንጽሕና ባለው እርሾ ነው እንጂ በአሮጌው እርሾ፥ በኀጢአትና በክፋት እርሾም አይደለም። 9ከዘማውያን ጋር አንድ እንዳትሆኑ በዚህ መልእክት ጻፍሁላችሁ። 10የዚህ ዓለም ዝሙት ብቻ አይደለም፤ ቀማኞችና ዘራፊዎች፥ ጣዖትን የሚያመልኩ ደግሞ አሉ፤ ያለዚያስ ከዚህ ዓለም ልትለዩ ይገባል። 11አሁንም ከወንድሞች መካከል ዘማዊ፥ ወይም ገንዘብን የሚመኝ፥ ወይም ጣዖትን የሚያመልክ፥ ወይም ዐመፀኛ፥ ወይም ተራጋሚ፥ ወይም ሰካራም፥ ወይም የሚቀማ ቢኖር እንደዚህ ካለ ሰው ጋር አንድ እንዳትሆኑ ጻፍሁላችሁ፥ እንደዚህ ካለው ሰው ጋር መብልም እንኳ አትብሉ፤ 12ምን አግዶኝ፥ በውጭ ባለው ላይ እፈርድበታለሁ? እናንተስ በውስጥ ከእናንተ ጋር የሚኖሩትን ፈርዳችሁ ቅጡአቸው። 13በውጭ ያሉትን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል፤ ይቀጣቸዋልም፤ ክፉውን ከእናንተ አርቁ።