ስለ እውነተኛ ጥበብ
6ለዐዋቆች ጥበብን እንነግራቸዋለን፤ ነገር ግን የዚህን ዓለም ጥበብ ወይም ያልፉ ዘንድ ያላቸውን የዚህን ዓለም ሹሞች ጥበብ አይደለም። 7ነገር ግን እግዚአብሔር አስቀድሞ ከዘመናት በፊት ለክብራችን የወሰነውን ተሰውሮም የነበረውን የእግዚአብሔር ጥበብ በምሥጢር እንናገራለን። 8የዚህ ዓለም ሹሞችም አላወቁትም፤ ይህንስ ቢያውቁ ኑሮ የክብር ባለቤትን ባልሰቀሉትም ነበር። 9ነገር ግን መጽሐፍ፥ “ዐይን ያላየው፥ ጆሮም ያልሰማው፥ በሰውም ልቡና ያልታሰበ እግዚአብሔር ለሚወዱት ያዘጋጀው ነው።” ብሎ የለምን? 10ለእኛም እግዚአብሔር በመንፈሱ ገለጠልን፤ መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔርን ጥልቅ ምሥጢሩን ያውቃልና። 11በሰው ልቡና ያለውን የሚያውቅ ሰው ማን ነው? በእርሱ ያለችው ነፍሱ ናት እንጂ፤ እንዲሁም ከእግዚአብሔር መንፈስ በቀር የእግዚአብሔርን አሳብ የሚያውቅ የለም። 12እኛ የዚህን ዓለም መንፈስ የተቀበልን አይደለም፤ ነገር ግን እግዚአብሔር የሰጠንን ጸጋ እናውቅ ዘንድ ከእግዚአብሔር የሚሆነውን መንፈስ ተቀበልን። 13ይህም ትምህርታችን ከሰው የተገኘ ትምህርት አይደለም፤ የአነጋገር ጥበብም አይደለም፤ መንፈስ ቅዱስ የገለጸው ትምህርት ነው እንጂ፤ መንፈሳዊ ጥበብም ከመንፈስ ቅዱስ የሚሆነውን መርምረው ለሚያውቁ ለመንፈሳውያን ነው። 14ለሥጋዊ ሰው ግን የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ይመስለዋልና፥ አይቀበለውም፤ በመንፈስም የሚመረመር ስለሆነ ሊያውቅ አይችልም። 15መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰው ግን ሁሉን ይመረምራል፤ እርሱን ግን የሚመረምረው የለም። 16የእግዚአብሔርን አሳብ ማን ያውቃል? መካሩስ ማን ነው? እኛ ግን ክርስቶስ የሚገልጠው ዕውቀት አለን።